Tuesday, September 30, 2014

እንዲሁ መውደድ….. እንዴት የተወደዳችሁ ሆይ አንድ ሰው ጌታውን የሚወደው ለምንድን ነው? ስለረዳው፣ ስላጸደቀው፣ ስለሰማው፣ ስለሚረዳው ወ.ዘ.ተ ሊሆን ይችላል፡፡ እንዲሁ ስለ መውደዱ ግን አስቦ አያውቅም፡፡ የአንድ አማኝ ልዩ ፍላጎቱ ወደ መንግስተ ሰማያት መግባት ነው ወይ መንግስቱን የሚሰጠውን ጌታን መውረስ ነው? እኛና እግዚአብሔር ያለን ግንኙነት በጥቅማችን ላይ ብቻ ከተንጠለጠለ ፍቅራችን ጉዳዩ ላይ አንጂ ሰጪው ላይ አይደለም ማለት ነው፡፡ይሄ ደግሞ እንከን ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ኢየሱስን የሚወዱት የጸጋን ትምህርት ባልተስተካከለ ሁኔታ ሲሰሙ ነው

እንዲሁ መውደድ….. እንዴት የተወደዳችሁ ሆይ አንድ ሰው ጌታውን የሚወደው ለምንድን ነው? ስለረዳው፣ ስላጸደቀው፣ ስለሰማው፣ ስለሚረዳው ወ.ዘ.ተ ሊሆን ይችላል፡፡ እንዲሁ ስለ መውደዱ ግን አስቦ አያውቅም፡፡ የአንድ አማኝ ልዩ ፍላጎቱ ወደ መንግስተ ሰማያት መግባት ነው ወይ መንግስቱን የሚሰጠውን ጌታን መውረስ ነው? እኛና እግዚአብሔር ያለን ግንኙነት በጥቅማችን ላይ ብቻ ከተንጠለጠለ ፍቅራችን ጉዳዩ ላይ አንጂ ሰጪው ላይ አይደለም ማለት ነው፡፡ይሄ ደግሞ እንከን ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ኢየሱስን የሚወዱት የጸጋን ትምህርት ባልተስተካከለ ሁኔታ ሲሰሙ ነው፡፡ ለተወሰኑት ጸጋ በኃጢአት ለመኖር ከጌታ ኢየሱስ ፍቃድ የሚቀበሉበት ኪዳን ይመስላቸዋል፡፡ ያለ ኢየሱስ ለኔ ወገን የለኝም የሚሉ ጥቅሶችን፣ ነቆራ አዘል አባባሎችን መጠቀም ይጀምራሉ፡፡ አይናቸውን ጨፍነው መዘመር ምናልባትም ከአይን ዘለላ እንባን ማውጣት ይጀምራሉ፡፡ በዚህ ወደ እግዚአብሔር እንደ ደረሱ ይሰማቸዋል፡፡ ነገር ግን ሁል ጊዜ ከስንፍናቸው ጋር፣ ከድፍረታቸው ጋር፣ ከስድባቸው ጋር፣ ከፍርዳቸው ጋር፣ ከንቀታቸው ጋር፣ ከአሽሙራቸው ጋር አሉ፡፡ ጌታን የወደዱት ጸጋ ስላለ ነው እንጂ ሰውን መውደዱ፣ ንጽሕናው፣ ከልብ የዋህነቱ፣ ትህትናው፣ ለሰው ሟች መሆኑ ነክቷቸው አይደለም/ለአንዳንዶቹ/ ፡፡ ምክንያቱም ከጌታ ሕይወት የቅድስና ፍንጣሪ ነክቷቸው አይታይም፡፡ ለነሱ ግን ኢየሱስ ልዩ ነው ከአብም ከመንፈስ ቅዱስም ይበልጣል፡፡እነዚህ ሰዎች ጌታ ኢየሱስን የወደዱት በኃጢአት ከሚወቅሳቸው ህሊናቸው ወቀሳ በነጻ ጸድቃችኋል የተባለው ትምህርት ስላሳረፋቸው ብቻ ነው፡፡ ቅዱሳንን የምንወዳቸው ስለሚያማልዱን በረከታቸው ስለሚደርሰን ብቻ ነውን ? ይሄ ባይሆን ልንወዳቸው እንችላለን? አንዳንድ ሰዎች አከሌ አያማልድም የሚል ትምህርት ሲያሸንፋቸው ከልባቸው ስፍ ስፍ ብለው ይወዱት የነበረውን ቅዱስ ወደ መጥላት ይመጣሉ፡፡ በጆሯቸው ስለዛ ጻድቅ መስማት አይፈልጉም፡፡ ያው ወደዋለሁ አከብረዋለሁ ብለው ከልባቸው ጥላቻ ለመሸሽ በአፋቸው ብቻ ይሞክራሉ፡፡ ግን የእግዚአብሔርን እንቁዎች እንዲሁም ቢሆን ለምን መውደድ አቃታቸው? ቀሪዎቹ አከሌ እንዲህ አድርጎልኛልና እርሱ ለእኔ ይቅርታ አድርጉልኝ እንጂ ከእግዚአብሔር በላይ ሆኖ ይታየኛል ሲሉ ሳያፍሩ ይናገራሉ፡፡ ወንጌል ሰብኮ ለንስሃ ስላበቃቸው ክርስቶስን በኑሮው ማሳየቱ አይነካቸውም ዲቪ በስለት ስላገኙበት ነው የወደዱት፡፡ እነዚህ ሰዎች የሞተውን ቅዱስ እንጂ በሕይወት ያለውን ጻድቅ አይወዱም፡፡ እንደ ያዕቆብ ልጆች ቅዱሱን ይገድላሉ መቃብሩን ያሳምራሉ፡፡ ማቴ 23፤29-30 በሕይወት ቅዱስ የለም ብለው ያምናሉ፡፡ ጻድቅ ድሮ ቀረ ባዮች ናቸው፡፡ በሕይወት ዘመኑ ለእግዚአብሔር ሃሳብ ያደረውን ቅዱስ ከቤተክርስቲያን እስኪወገድ ድረስ ያሳድዱታል፡፡ እንደ ቀድሞዎቹ አይሁድ የክስ ዝርዝራቸው አያልቅም፡፡ ዛሬ ያለው የእግዚአብሔር ሰው አይረባም፡፡ እግዚአብሔርን ፈርተው እንጂ የዛሬው እግዚአብሔር ራሱ እንደ ድሮው አይደለም ለማለት ሁሉ ይፈልጋሉ፡፡ የዛሬው ቅዱስ ምዕመን፣ ጳጳስ፣ ሰባኪ፣ ዘማሪ፣ አስተናባሪ ፣ መካሪ፣ ሰንበት ተማሪ ምንም ረብ የሌለው ተራ ነው፡፡ የሞቱት ግን ስለሚጠቅሟቸው የከበሩ ናቸው፡፡ ባይጠቅሟቸው ግን እነርሱንም አይጠቅሙም ባይ ይሆኑ ነበር፡፡ስለዚህ በስሙ የምታመኑ ሆይ ከጌታችን ከመድሃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ከከበረው መምህር አባት እንዲሁ መውደድን ልንማር ይገባል፡፡ አንድ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን አንዲሁ ወዷል፡፡ዮሐ3፤16 ተብሎ ተጽፏል፡፡ እግዚአብሔርም ስለጠቀመን ብቻ ሲወደድ ደስ የሚለው አይመስለኝም፡፡ ጻድቁም ስለጠቀመ ብቻ ከተከበረ ደስ የሚለው አይደለም፡፡ ጥቅሙ በረከቱ ዳረጎት ሆኖ ይሰጣል፡፡ በእምነት የሆነ ፍቅር በነጻ የሆነ መውደድ እጅግ ደስ ያሰኛል፡፡ያለ እምነት የሆነ ሁሉ ኃጢአት ነው፡፡ሮሜ 14፤23 እባካችሁ ለሌሎች ሼር አድርጉት

Wednesday, September 24, 2014

ሰላም ለሁላችሁ፤- መስቀል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማንን ተሸክሞ በእንጨት መስቀል መሰቀሉን የምናስብበት ነው

ሰላም ለሁላችሁ፤- መስቀል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማንን ተሸክሞ በእንጨት መስቀል መሰቀሉን የምናስብበት ነው፡፡ ገላ 3፤13 መሰቀሉ የጌታን አሸናፊነት ያሳየ ነው፡፡ ክርስቶስ ገዳዮችን ብቻ ሳይሆን ሞትን የተዋጋ ነጻ አውጪ ነው፡፡ በመስቀል ሲሞትም እየማረከ ከፍ እያለ ነበር እንጂ እንደ ሰው እያለቀለት አልነበረም፡፡ ምክንያቱም ትግሉን በትንሳኤ ደምድሞታል፡፡ ስለዚህ ሞቱን ክብር ብሎ ጠርቶታል፡፡ ዮሐ 17፤2 መሰቀሉም ወደ ላይ ከፍ ማለቱ ነበር፡፡ ተሰቀለ ከፍ ከፍ አለ ማለት ነው፡፡..እኔም ከምድር ከፍ ከፍ ያልሁ እንደሆነ ሁሉን ወደ እኔ እሰበስባለሁ..ዮሐ 12፤32 እንዳለ፡፡ እኛም በመሰቀሉ ወደ ላይ ክፍ ብለናል፡፡ ወደ ፊት ወደ እርሱ ለመነጠቅ ከበጉ ሰርግ ለመታደም በተስፋ የምንጠብቅበትን መግባት አግኝተናል፡፡ ምልክቱ የእግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነው … ለብዙዎቹ ለመውደቃቸውና ለመነሳታቸው ለሚቃወሙትም ምልክት ሆኖ ተሹሟል…ሉቃ 2፤35 መስቀሉም በጉ የተሰዋበት ቅዱስ መሰዊያ ነው፡፡ ያዳኛችንን ቅዱስ ሞት የምናስብበት ነው፡፡ መልካም የመስቀል በዓል ይሁንላችሁ፡፡ እባካችሁ ለሌሎች ሼር አድርጉት www.ashenafigmariam.blogspot.com

Friday, September 19, 2014

ሰላም ለሁላችሁ፤- ምህረቱ ለሚፈሩት እስከ ትውልድ ትውልድ ነው…ሉቃ 1፤50 በእግዚአብሔር የተወደዳችሁ ሆይ፤- እግዚአብሔርን በፍቅር መፍራት ስለእርሱ ከማወቅ ይጀምራል፡፡ ጌታችሁን የምታውቁት ስለርሱ ፍላጎትና ፍለጋ ሲኖራችሁ ነው፡፡ በርግጥ አሁን ያላችሁበት ኑሮ የማንንም እርዳታ የማይፈልግ ይሆናል፡፡ ጊዜአችሁን ምቾታችሁን ሊያስጠብቅላችሁ ይችላል በምትሉት ነገር ብታጠፉ ደስ ይላችኋል፡፡ ነገር ግን እናንተ የዛሬው ሰዎች ብቻ አይደላችሁም የምድርም ኑሮ ብቻ አይደለም ያላችሁ፡፡ትውልዳችሁን የሚረከብ ጌታ አለ፡፡ ዘላለም የሚባል ዓለም አለ፡፡ ወደዛ የምትደርሱበት መንገድ ጌታ ነው ፡፡ ለትውልዳችሁ የምታወርሱት ከምድር የሆነ ጌጠኛ ድንጋይ ብቻ መሆን የለበትም፡፡ እንደ አብርሃም የዘላለም ምህረት የመለኮት ጥበቃ ለልጆቻችሁ ማቆየት አለባችሁ፡፡ ይህን የምታገኙት ልዑሉን ስታውቁትና ስትፈሩት ነው፡፡ ለትውልዳቸው ርግማን ትተው ያለፉ የትናንት ሰዎች ነበሩ፡፡ የሰው ደም በከንቱ ያፈሰሱ፣ በድሃ እንባ የታጠቡ፣ ሃገር ያፈረሱ፣ ልዑሉን የረገሙ፣ ማምለኪያውን ያቃጠሉ፣ በጉቦ የፈረዱ፣ ባይተዋሩን ፊት የነሱ… እነዚህ መርገምን ለትውልዳቸው ትተው ሄደዋል፡፡ የፈሩት ግን ተመርቀዋል ከነልጆቻቸው ምህረትን ጠግበዋል፡፡የጥበብ ሁሉ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው ምሳ 1፤7 ተባረኩ፡፡ እባካችሁ ለሌሎች ሼር አድርጉት visit www.ashenafigmariam.blogspot.com

Tuesday, July 8, 2014

ሰላም ለሁላችሁ፤- አገልግሎት ፍላጎት ነው ወይስ ቅባት?

ሰላም ለሁላችሁ፤- አገልግሎት ፍላጎት ነው ወይስ ቅባት? ዛሬ ብዙ ሰው መናገር ስለሚቻል ሰባኪ እንደሚኮን ትንሽ የማይሻክር ድምጽ ካለ መዘመር እንደሚቻል የሚያስቡበት ጊዜ ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ አርቲስቱና ዘፋኙ በትርፍ ሰዓቱ ዘማሪ ነው፡፡ በክብረ በዓላት ቀን ደግሞ ቅልጥ ያለ ጨፋሪ ሆኖ ይቆማል፡፡ በትርፍ ሰዓትሽ ምን ያደስትሻል ተብላ አንዲት አርቲስት በቀደም እሁድ በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ተጠየቀች፡፡ ለስለስ ያለሙዚቃ በተለይ የሚያስጨፍር ከሆነ ምድር አይበቃኝም አለች፡፡ ይህችው ሴት ለቤተክርስቲያን መርጂያ መዝሙር ዘምራ/ ለቤተክርስቲያ ያረገችውን መልካም ስራ ባደንቅም/ በየቤተክርስቲያኑ መድረክ አትጠፋም፡፡ አንዳንዴም ቤተክርስቲያን ተደፈረች ድረሱ የሚል ሃሳብ ወለድ ድራማዎችን እየሰሩ የእነሱ መቅደስ /ሰውነታቸው/ ዓለምን የሚያገለግልና ውሳኔአቸውም ለእግዚአብሔር ያልተሰጠ ሆኖ ይታያል፡፡ አንዱ አርቲስት ቀደም ብሎ ጥሩ የሚባል ዝማሬ ሰራ፡፡ ቆየት ብሎ በአንድ መጽሔት እኔ ዘማሪ መሆን አልፈልግም ቤተክርስቲያንን ለመርዳት ነው! ብሎ ቃለምልልስ ሰጠ፡፡ እግዚአብሔር ጉሮሮ ሳይሆን ልብ ነበር የሚያስፈልው፡፡ የሚቃጠል መስዋት ደስ አያሰኝህም የእግዚአብሔር መስዋት የተሰበረ ልብ ነው፡፡ መዝ50፡17 አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት የተቀቡ ለዚህ አገልግሎት ራሳቸውን የሰጡትን ዘማሪያንን አይናችሁ ላፈር ብለው እኒሁ የሁለት ቤት ሰዎችን ልዩ አገልጋያቸው አድርገው ይሰይማሉ፡፡ ማንም ሰው ለጌታው ክብር ሊሰጥ እንደሚገባ አምናለሁ፡፡ ነገር ግን አውደ ምህረቱና መቅደሱ እግዚአብሔር በጸጋው ቅባት በለያቸው ሰዎች ነው መገልገል ያለበት፡፡ የእግዚአብሔር የሆነ ልዩ ነገር ከሌለ ቅድስና እንዴት ይለያል? የተነሳ ሁሉ ነፍሱን ለጌታው ብቻ ወስኖ ሳይሰጥ ላገልግል ካለ ዓለማዊነት ሰተት ብሎ ወደ ቤተክርስቲያን ይገባል፡፡ቤተክርስቲያ የምትጠፋበት ዋናው መንገድ ዓለማዊነት መንፈሳዊ ለምድ ለብሶ ሲገባባት ነው፡፡ በምዕራቡ ዓለም ያሉ ዘፋኞች በድምጻቸው ብቻ ዘማሪዎች ነበሩና ትንሽ ከፍ ሲሉ የተደቁ ዘፋኞች ወደ መሆን ይቀየራሉ፡፡ እድገቱ ከዘማሪነተት ወደ ዘፋኝነት የሆነ ይመስል ያኔ የሰንበት ተማሪ ዲያቆን ነበርኩ ይሉናል፡፡ ማንም ይህን ሆኖ ከሆነ ዘፋኝ የሆነው እንዲህ ብሎ በመናገሩ ማፈር አለበት፡፡ እግዚአብሔር በቂ እንጀራ ነው፡፡ እግዚአብሔር ትልቅ ጥበብ ነው፡፡ እርሱ የዚህ ዓለም ጥበብ የማይደግፈው ራሱን የቻለ ብልጥግና ነው፡፡ሰው ወደ እግዚአብሔር የሚመጣው ጌታን ሊያግዝ ሳይሆን ራሱን ሰው አድርጎ ሊሰራ ነው፡፡ ፈርቶ፣ ትሁት ሆኖ፣ ለመናገር ሳይቸኩል ደግሞም በእምነት አድጎ ዓለሙን ርግፍ አድርጎ ሊኖር መሆን አለበት፡፡ አገልግሎትም በቅባት እና በመጠራት እንጂ በታለንት ወይ በችሎታ አይደለም፡፡ በመንፈሴ እንጂ በሐይልና በብርታት አይደለም ይላል የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር፡፡ ዘካ 4፤6 ከእናንተ ብዙዎች አስተማሪዎች አይሁኑ የባሰውን ፍርድ እንድንቀበል ታውቃላችሁና፡፡ ያዕ 3፤1 እባካችሁ ለሌሎች ሼር አድርጉት

Tuesday, May 27, 2014

ከቤተክርስቲያን ውጪ ትምህርት?......./ቀሲስ አሸናፊ ገ/ማርያም/

ከቤተክርስቲያን ውጪ ትምህርት?......./ቀሲስ አሸናፊ ገ/ማርያም/ ከተራራው በወረደ ጊዜ ብዙ ህዝብ ተከተሉት ማቴ 8፤1 ይህ ምንባብ ጌታ በተራራ ካስተማረ በኋላ ተራራ መውጣት ያቃታቸውን ብዙ ህዝብ ከተራራው በታች እንዳገኘ ይገልጣል፡፡ የልዕልናና የክብር ከፍታ ባለቤት ነችና ተራራ ቤተክርስቲያን ነች፡፡ ሆኖም አማኞች ሁሉ አንድ ሳይቀሩ ወደ ቤተክርስቲያን በመሄድ የጸጋውን ሚስጢራት የሚካፈሉ አይደለም፡፡ ከተለያየ ድካማቸው ጋር ዓለም ላይ ከግርጌ እንደተበተኑ አሉ፡፡ ቤተክርስቲያን አሁን ባለችበት ሁኔታ ልጆቿን ማስተማር ያለባት በቤተክርስቲያን ቅጥር ብቻ ነው የሚሉ ተከራካሪዎች አሉ፡፡ ሃሳባቸውን አከብራለሁ፡፡ ነገር ግን ያለንበትን ነባራዊ ሁኔታ ስንመረምር አስተሳሰቡ እጅግ ጠበብ ያለ ሆኖ ይታያል፡፡ ምክንያቱም ቤተክርስቲያን ስትመሰረት ሐዋርያት ምኩራብ ቁጭ ብለው ወንበር ዘርግተው ሰብከው ሳይሆን ሄደው ወጥተው ፣ ሮጠው ወድቀው ተነስተው ነው፡፡ የባህር ሞገድ እየመታቸው መርከባቸው እየተሰበረ፣ ከአውሬ ጋር እየታገሉ ከሮም እስከ እስፔን ከእስያ እስከ አፍሪካ ተሰደው ነው፡፡በዘመኑ እግር ያላት ቤተክርስቲያን ነበረችና ከሮማውያን ርኩሰትና ከግሪክ ፍልስፍና የእግዚአብሔርን በጎች ነጥቃ ወደ ሰማያዊ ጥሪ አድርሳለች፡፡ ቀድሞም የቤተክርስቲያን ራስ እና አስተዳዳሪ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሂዱና አህዛብን ሁሉ በአብ በወልድ እና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁ ደቀ መዛሙርቴ አድርጉ ብሉ አዟል፡፡ሂዱ የሚለው ትዕዛዝ ተቀምጣችሁ ጠብቁ ከሚል ሃሳብ ፍጹም ተቃራኒ ነው፡፡ ማቴ28፤19 ወንጌል መሰበክ ያለበት ወዳጆቼ እንደሚያምኑበት በቤተክርስቲያን አውደ ምህረት መሆኑ ዋንኛ ነገር ነው፡፡ ነገር ግን ቤተክርስቲያን ያልመጣውስ? ካለማወቅ የተነሳ ሃይማኖት ዝም ብሎ ማህበራዊ ልማድ ብቻ ነው ብሎ የቆመውስ? በዓለም ወለድ ፍልስፍና ታስሮ የመስቀሉን ቃል ሳይሰማ በሥጋ የሚኖረውስ? በየዋህነቱ ብቻ ኖሮ ለበላተኞች ራት ለመሆን ጫፍ የደረሰው? ይህን ሁሉ ደካማ መንጋ ማነው የሚያተርፈው? ወንጌል ለቆራቢው ስብከት ቤተክርስቲያን ለሚተጋው ምዕመን ብቻ ከሆነ ሸክም የከበደበት ደካማው ዕጣው ምንድነው? ያላመኑስ እንዴት ወንጌል ሊሰሙ ይችላሉ? ስለዚህ ወንጌልን በሁለቱም መንገድ በተደራጀ ሁኔታ ልናዘጋጅላቸው ተገብቷል፡፡ 1- ቤተክርስቲያን መምጣት ለቻሉ፡- ቤተክርስቲያን የመጡ ወደ እግዚአብሔር እንዲመጡ ወንጌላችን ልትረዳቸው ይገባል፡፡ በየክብረ በዓላቱ በወርና በዓመት አባቶቻችን በሰሩት ቅዱስ ስርዓት መሰረት ሰዎች ያለምንም ቀስቃሽ ወደ ቤተክርስቲያን ይመጣሉ፡፡ እነዚህ መንጎች በተሰናዳ ወንበር በተረጋጋ መንፈስ እነሱ ባሉበት ደረጃ ህይወታቸውን ከአምላካቸው ጋር ሊያጣብቅ የሚያስችል ትምህርት ያስፈልጋቸዋል፡፡ ዝናብ ቢመጣ ያለምንም ክፍያ የሚሰበሰቡበት ንጹህ አዳራሽ ሊኖራቸው ይገባል፡፡ የምክር አገልግሎት ሊያገኙ የሚችሉባቸው የተለዩ ክፍሎች ሊዘጋጅላቸው ይገባል፡፡ ከንስሃ አባቶቻቸው ጋር ሚስጢራቸውን የሚያወሩባቸው ከለል ያሉ ቦታዎች ያስፈልጋቸዋል፡፡ ሕጻናቶቻቸው አማርኛ ወይ ሌላ ሃገር በቀል ቋንቋ ተናጋሪዎች ከሆኑ እንዲሁም በከተሞች የሚኖሩ ከሆነ እንግሊዝኛ፣ ፈረንሳይኛ እንዲሁም አዲሱን አማርኛ የሚናገሩ መምህራን እንዲያገኗቸው ልዩ መርሃ ግብር/እንደቦሌ መድሐኒዓለም/ ሊዘጋጅላቸው ይገባል፡፡ ከተገኙም አለቆች እና የአውደ ምህረት ገምጋሚዎች እንዲደነቁ ተብሎ ሳይሆን ህዝቡ በሚገባ እንዲገባው እና እንዲመሰረት ማድረግ የሚችል ትምህርት በተለይ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት/ጥናት/ ሊቀርብላቸው ይገባል፡፡ በቤተክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስን አንድ በአንድ ምዕራፍ በምዕራፍ ማስተማር ከጀመርን በጎቹ ከውጭ በሚሰሙት አዲስ ስብከት አይደነቁም፡፡ በቤታችን ሰምተነዋል እናውቀዋለን ብለው ጸንተው ይቆማሉ፡፡እንዲሁም ልዩነትን የሚጸየፉ አንድ አይነት መንፈሳዊነት ያላቸው ያደርጋቸዋል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሰውን አንድ ዓይነት በማድረግ የተለየ መጽሐፍ ነው፡፡ ራሳቸውን የሚከላከሉበት ቁንጽል ጥቅስ ብቻ ሳይሆን ጥያቄዎቻቸውን አደላድለው እንዲያውቁ ማድረግ እንችላለን፡፡ሌላውን ለመርታትና ለማሳመን ብቻ ሳይሆን ራሳቸው እንዲያምኑ አድርጎ መስራት ይጠበቅብናል፡፡ 2- ከቤተክርስቲያን ውጪ፤- ከቅጥሩ ውጪ ያለው ህዝብ ብዙ ነው፡፡ በምክንያት የታሰረ፣ አውቃለሁ የሚል፣ በዓለም እና በአጋንንት አሰራር የተያዘ፣ እንዲሁ ተፈጥሮአዊ ሰው የሆነ፣ ያላመነ ያልተጠመቀ…….. እጅግ ብዙ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን አስተምራ አምና የመረቀቻቸው፣ ክህነት ድቁናና ቅስና የሰጠቻቸው፣ በጸጋ እግዚአብሔር ሰባኪ ሆነው የተለዩ ስብከቶቻቸውን የአውደ ምህረት ብቻ አድርገው ሊያዘጋጁ አይገባም፡፡ በለቅሶ ቤት፣ ሰርግ ቤት፣ ምዕመናን ቤት/ቤተሰባዊ ጉባኤ/፣ እንደ ፊሊጶስ /በሰረገላ /መጓጓዣ ውስጥ፣ ሴተኛ አዳሪዎች በሚሰበሰቡባቸው ቤቶቻቸው፣ ሰራተኞች ስራ ፍለጋ በጠዋት በሚኮለኮሉባቸው አደባባዮች፡፡ ሊስትሮ እያስጠረጉ ለሊስትሮዎች፣ በገበያ ስፍራዎች፣ ለገበሬው በእርሻ ስፍራው በጽዋ ማህበራት፣ በሆስፒታል ይህን በመሰለ ቦታ የመዳን ወንጌል እንዲሰሙ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ ጌታ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር እንደዚህ ነው የሰበከው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም የሐይማኖታችንን ሐዋርያና ሊቀ ካህን ኢየሱስን ተመልከቱ ብሎናል፡፡ዕብ 3፤1 በዚህ መንገድ ካልሰራን ከጥቂት ዓመታት በኋላ ቤተክርስቲያን እንደ አውሮፓውያን አብያተክርስቲያናት የአረጋውያን ብቻ መሰብሰቢያ ልትሆን ትችላለች፡፡ መሪዎቿና ልጆቻቸው በቋንቋ እና በመረዳት/understanding/ የማይግባቡ በመካከላቸው ያለው ድልድይ የሰፋ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ቤተክርስቲያንም ይህን ተልዕኮ እየተቆጣጠረች ልትመራ ይገባታል፡፡ በዚህ መንገድ የስህተት ትምህርታቸውን በማስተማር ከመንጋው ለይተው ሜዳ የሚጥሉ ሰነፎች በዓለም በብዛት አሉና፡፡ በውጭ ያሉትን ካስተማሩ በኋላ ወደ በረቱ ማስገባት ግዴታ ነው፡፡ ሰብዓ ሰገልን የመራው ኮከብ ቤተልሔም አድርሷቸው እንደተሰወረ አገልግሎታችን በጎቹን አምጥቶ ለሞተላቸው ጌታ በቤቱ ማስረከብ አለበት፡፡ማቴ 2፤9 ምክንያቱም ጸጋው የሚገኝባቸው ሚስጢራት ማለትም ጥምቀት ቅዱስ ቁርባን ተክሊል ወ.ዘ.ተ በውጭ የማይፈጸሙ ናቸውና፡፡ ይህ ብቻ አይደለም ከውጭ የሚገቡት ውስጥ ከሚጠብቋቸው ምዕመናን ጋር መንፈሳዊ ህብረት መፍጠር አለባቸውና ነው፡፡ህብረቱ እስከ ጽዮን ተራራ እስከ ሰማይ የሚደርስ ነው፡፡ ይቆየን፡፡ዕብ 12፤22 ጌታ ሆይ ጉልበታችንን አበርታ እባካችሁ ለሌሎች ሼር አድርጉት

Wednesday, April 30, 2014

የምትወዱአቸውን ግደሏቸው

የምትወዱአቸውን ግደሏቸው ጌታ እግዚአብሔር ሲፈጥረን ልባችንን አስፍቶ ነው፡፡ እንውደድ ካልን ብዙ ሰዎችን እንወዳለን፡፡ የሰውን ህይወት ከሚገዙ ሁለት ነገሮች አንዱ ፍቅር ነው፡፡ ህግም እግዚአብሔር አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህ በፍጹም ሃይልህም በፍጹም ሃሳብህ ውደድ እና ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ በሚሉ ሁለት ትዕዛዞች ተጠቅልሏል፡፡ሉቃ 10፤27 ስለዚህ የሰው ነፍስ በሁለት ፍቅሮች መካከል ትኖራለች፡፡ እግዚአብሔርን የምንወድበት ፍቅር በፍጹም ነፍስ፣ ሃይል፣ ልብ እና ሃሳብ ነው፡፡ ይሄ ፍቅር በተፈቃሪው/በጌታ/ ላይ ይታመናል ተስፋ ያደርጋል ምንጊዜም የማይጥል እንደሆነ አስቦ ይደገፍበታል፡፡ከራስ በላይ ይወዳል ምናልባት ምቾትን ጥሎም ቢሆን ቅር አይለውም፡፡ ጌታም እንዲህ ከወደዱት አይጥልም፡፡ ፍቅሩም ለዘላለም ነው፡፡ አለኝ ቢሉት ይኖራል እርሱ ያውቃል ቢሉት ያውቃል፡፡ ቢወራረዱበት ይረታል፡፡ እወቁልኝ ቢሉት አያሳፍርም፡፡ ሰውን ግን በዚህ አይነት መንገድ መውደድ ጉዳት ያመጣል፡፡ ያልታዘዘም መንገድ ነው፡፡ ሰው የሚወደደው እንደራስ ነው፡፡ ለሰው የምታደርጉትን ነገር ከራሳችሁ አንጻር እስቲ እዩት፡፡ ትንሽ ልጅ ተርቦ ብታዩ በልባቸችሁ የኔ ልጅ ቢሆንስ ስትሉ የበለጠ ትራራላችሁ፡፡ የሰው ኃጢያት ተገልጦ በአደባባይ ሲዋረድ ብታዩ እኔ ብሆንስ ስትሉ እጅግ ታዝናላችሁ፡፡እኔ እንደምሞት እርሱም እኮ እንዲሁ ነው ትላላችሁ፡፡ እንደራስ መውደድ እንዲህ ነው፡፡ አንዳንድ ግዜ ግን ሰው ሰውን በፍጹም ነፍስ በፍጹም ልብ በፍጹም ሃሳብ በፍጹም ሃይል መውደድ ይጀምራል፡፡ ስለዚህ ተስፋ መመኪያ ያደርገዋል፡፡የማይሳሳት ፍጹም አድርጎ ያስበዋል፡፡ ስህተቱን በሚያዩ ሰዎች ላይ ቂም ይይዛል፡፡ ያለእርሱ መኖር አልችልም ብሎ ያብዳል፡፡ የሞተ እንደሆነ ገመድ አቀብሉኝ እንዴት እኖራለሁ ወይ አብሬ እቀበራለሁ ተውኝ ብሎ ለያዥ ያስቸግራል፡፡ እርሱ ከተቀየመ ሰማይ የተደፋበት ያክል ተስፋ ቢስ ይሆናል፡፡ አንድም ቀን ይሞታል ብሎ አያስብም፡፡ ከእግዚአብሔር ዘላለማዊነት ጋር አመሳስሎ የማይወድቅ ትምክት አድርጎ ይቆጥረዋል፡፡እርሱ ካለኝ ምን ሆናለሁ ይላል፡፡ ወደ እግዚአብሔር ከሚጸልይባቸው ደቂቃዎች ይልቅ ለዚህ ሰው ችግሩን የሚነግርባቸው ሰዓቶች እጅግ ብዙ ናቸው፡፡ ቤቱን በሰው አጥንት ግድግዳውን በሰው ሥጋ ያጠረ ሰውን ይመስላል፡፡አቤት ይሄ ሰው ውድቀቱ! ይህ ሰው ልቡ የተሰበረ እለት ለመጠገን በጣም አስቸጋሪ ይሆናል፡፡ ትምክህቱን ሲነጠቅ መኖሩም አብሮ ይጠፋል፡፡ እርሱ ሙሉ ሰው ሆኖ ሳለ ራሱን እንደ ማይጠቅም አድርጎ ይቆጥራል ለከፍተኛ የስነልቦና ችግር ይጋለጣል፡፡ እባካችሁ የምትወዷቸውን ሰዎች በአእምሮአችሁ ግደሏቸው፡፡ አናቴ ብትሞት? አባቴ ቢሞትስ ?ፍቅረኛዬ ወይ ሚስቴ ወይ ባለቤቴ ቢሞትስ ? ልጄ ቢሞትስ? ያ ችግር ሲገጥመኝ እየተሯሯጠ የሚያግዘኝ ባለስልጣን ወዳጄ ቢሞትስ? እኔ ካለሁ አይዞህ ያለኝ አጎቴ ድንገት ቢያንቀላፋስ……. መኖር እችላለሁ? በሉ እስቲ! ጌታ ለተከታዮች እንደሚሞትና በሶስተኛው ቀን እንደሚነሳ ይነግራቸው ነበር፡፡ እነሱ ግን አላስተዋሉም፡፡ ሁሌ መኖር ያለ ይመስላቸው ነበር፡፡ማር 9፤9 ጌታችን አስቀድሞ በወዳጆቹ አእምሮ ሞቱን አትሞ ነበር፡፡ የምትወደዱ ሰዎችም አንድ ቀን እንደማትኖሩ ለሚወዷችሁ ንገሩ፡፤ ዝም ብላችሁ አትኑሩ፡፡ ለህጻናት ልጆቻችሁ እንኳ እኔ አንድ ቀን እሞታለሁ የማይሞተው አምላክ አሳዳሪ በሰማይ አለላችሁ እንዳትፈሩ በሏቸው፡፡ አለሁ እያላችሁ እንዳታልሏቸው፡፡ የአብ ጸጋ የወልድ ፍቅር የመንፈስ ቅዱስ አንድነት ይጠብቃችሁ

Monday, March 31, 2014

ሰላም ለሁላችሁ፤- እስቲ ተናገሩ፡-

ሰላም ለሁላችሁ፤- እስቲ ተናገሩ፡- እናት አባት ሳይኖራችሁ ሰው ከወላጅ ሊቀበለው የሚገባውን ፍቅር ተርባችሁ ስታድጉ ወላጅ ሆኖ እየሞላ ሳያጎድል ያሳደጋችሁ እግዚአብሔር አይደለም? እስቲ ተናገሩ፤- መልካም ያላችሁት ሰው ባስቀመጣችሁት ቦታ ሳይገኝ፣ ሚስጢራችሁን አውቆ ሲሳለቅባችሁ ልባችሁ ተሰብሮ ሳለ መንፈስ ቅዱስ ደርሶ ትናትን አላስረሳችሁም? ኑሮዬን ከርሱ/ሷ ጋር አድረጋለሁ ብላችሁ ብዙ ዋጋ የከፈላችሁበት ትዳርና ጓደኝነት ገደል ገብቶ በራችሁን ዘግታችሁ ስታለቅሱ መጥቶ እንባችሁን ያበሰ ጌታ አልነበረም? እስቲ ተናገሩ፤- ሞት ከደጃችሁ የቀረበ እስኪመስላችሁ በብርቱ ታማችሁ በራሳችሁ ተስፋ ቆርጣችሁ ሳለ ቆማችሁ እንድትሔዱ የሆናችሁት በአምላካችሁ እጅ አይደለምን? ውስጣችሁ ከተቀበረ አሳዛኝ ታሪካችሁ ጋር የተቀበላችሁ ጌታ ኢየሱስ አይደለምን?ማቴ 11፤28 ተለወጠ ስትሉት ሳይለወጥ ተወኝ ስትሉት ሳይተው ተቆጣ ስሉት ወዶ… ያሳደራችሁ መልካም አሳዳሪ ጌታችሁ አይደለምን ?እስቲ ተናገሩ፡- በእዳ ተይዛችሁ እዳችሁን የከፈላችሁበት፣ ተገፍታችሁ የፈረደላችሁ፣ ዲዳ ናቸው ብለው ሲከሷችሁ የተናገረላችሁ፣ እንዴት እኖራለሁ ብላችሁ ያኖራችሁ እንዴት እለምዳለሁ ብላችሁ ሃገር ያስለመዳችሁ እንደጥላ የሚከተላችሁ እግዚአብሔር አይደለምን…….pls share it ብቸኝነቴን ያስረሳኝ ወላጅ ደጋፊ የሆነኝ ሰላላ ክንዴን ያበረታ እርሱ ብቻ ነው የኔ ጌታ ይፍሰስ እንባዬ ይሙላኝ አንክሮ ፍቅሩ ሲነካኝ ዓለቴን ሰብሮ አለ በልቤ የእርሱ መብራት መልካምነቱን የማይበት ዘማሪ ዳዊት በቀለ ቁ 2 /በቅርብ የሚወጣ ዝማሬ/

Friday, March 28, 2014

battery low- ሃይል አለቀ የእጅ ስልካችን ቀን ከተጠቀምንበት በኋላ ማታ ሃይል አለቀ/ battery low/ ይለናል፡፡ እኛም ከሃይል ጋር አገናኝተን እንሞላዋለን፡፡ ነፍሳችንም እንደዚህ ስልክ ነች፡፡

battery low- ሃይል አለቀ የእጅ ስልካችን ቀን ከተጠቀምንበት በኋላ ማታ ሃይል አለቀ/ battery low/ ይለናል፡፡ እኛም ከሃይል ጋር አገናኝተን እንሞላዋለን፡፡ ነፍሳችንም እንደዚህ ስልክ ነች፡፡ ትደክማለች፡፡ ከሃይሏ ከተለያየች battery low ትላለች፡፡በጋለ ፍላጎት እናመልክ ከነበረ መንፈሳችን ሙትት ይልብናል፡፡ መጸለይ አሰልቺ ሥራ ይሆንብናል፡፡ ቃል ወደምንሰማበት ጉባኤ ለመሄድ ፍላጎት ስለምናጣ አገልግሎቱን እንተቻለን፡፡ ምን እነሱ ሰዓት አያሳጥሩ! የሚሰብኩት በግዕዝ ነው አይገባ! ወ.ዘ.ተ. ቅያሜ ለበስ ንግግሮች እናበዛለን፡፡ ይሄኔ ነፍሳችን battery low እያለችን ነው፡፡ ጓደኞቻችን ስለፓለቲካ፣ ስለኳስ ፣ ስለጌጣጌጥ የሚያወሩ ብቻ ቢሆን ደስ ካለን፣ መንፈሳዊ ሃሳብ ካላቸው ባልንጀሮቻችን ጋር ያለንን ግንኙነት ማቋረጥ ከወደድን ሃይላችን እያለቀ መሆኑን ያሳያል፡፡ በዓመቱ ውስጥ ያነበብናቸው መጽሐፍት ፍልስፍናና ልብወለድ ብቻ ከሆነ ብዙ ጊዜያችንን ሙዚቃ በማዳመጥ ካሳለፍን ድሮ የነበረን የሞቀ ልባችን ከቀዘቀዘ battery low እያለን ነው፡፡ ወንጌልን በመረዳት ስም ከተግባራዊ አምልኮ ማለትም ለብርቱ ጾም፣ ከጸሎት፣ ድሆችን ከመጎብኘት፣የተቀቡትን ከማክበር ፣ ንስሃ ገብቶ በራስ ስንፍና ከመጸጸት ይልቅ በቃል መደባደብን ከመረጥን ቀይ መብራት እያበራን ነው፡፡ ሌሊት ተነስቶ ማስቀደስን ከተውን፣ ለራሳችን ልዩ ጊዜ ካጣን፣ ከንስሃ አባቶቻችን ጋር የመገናኘት ፍላጎታችን ከሞተብን ነፍሳችን ባትሪ እየጨረሰች እንደሆነ ማሳያ ነው፡፡ ወርቃማ የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ትምህርትና ህይወት ትኩር ብሎ መመልከት ካቃተን፣ ስዕሉ ከህሊናችን ከጠፋ ይህ በመሆኑም ምንም ካልመሰለን ወደ ራሳችን ማየት እንዳለብን ማስጠንቀቂያ ነው፡፡ሁሌ ትችትና ንቀት የተሞላ ሃሳብ ከልባችን ከወጣ ልባችን ታውቃለህ፣ ትበልጣለህ፣ ሌሎች ግን አይረቡም፣ አያውቁም፣ አልተረዱም ካለን battery low እያለን ነው፡፡የዓሳ አጥማጁን የጴጥሮስን የዋህ ልብ ጥለን የመጽሐፍት ሸምዳጁን የቀያፋን ልብ በውስጣችን ካገኘን አደጋ ላይ ነን፡፡ መቅረዙ የተወሰደበት መብራቱ የጠፋበት ሰው ሆኖ መኖር ምቾት ይሰጣል? በሞተ ህሊና በደነዘዘ ልብ መመላለስ ያስደስታል? የድንኳናችን/ሰውነታችን/ መብራት ጠፍቶ እስከመቼ ይኖራል? እንግዲህ ከወዴት እንደወደቅክ አስብ ንስሐም ግባ የቀደመውንም ስራህን አድርግ፡፡አለዚያ እመጣብሃለሁ ንስሐም ባትገባ መቅረዝህን ከስፍራው እወስዳለሁ፡፡ ራዕ 2፤5

Thursday, March 20, 2014

ፍለጋ ወ ስርቆት /ዘማሪ ቀሲስ አሸናፊ ገ/ማርያም/ ጥቂት የማይባሉ ወንዶች ትዳርን በሩቁ በመፍራት ተመሳሳይ ናቸው፡፡

ፍለጋ ወ ስርቆት /ዘማሪ ቀሲስ አሸናፊ ገ/ማርያም/ ጥቂት የማይባሉ ወንዶች ትዳርን በሩቁ በመፍራት ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ቶሎ ማመን ይቸግራቸዋል፡፡ ሴቶቹ በአብዛኛው አታላዮችና አስመሳዮች እንደሆኑ ይገምታሉ፡፡ መልካም ሚስት በቀላሉ አትገኝም በማለት ወደ ራሳቸው ሰው ሰራሽ የፍለጋ ዘዴ ይገባሉ፡፡ ፍለጋ ሲወጡ ራሳቸው የፈጠሯትን ሴት እንጂ እግዚአብሄር የሰራትን አይመለከቱም ፡፡ አይኗ ጎላ ጎላ ያለ፣ የእጅና እግር ጣቷ ረጃጅም የሆኑ…… ወዘተ ብለው ይነሳሉ፡፡ በአጋጣሚ ካገኛት አንዲት ሴት ጋር ቀጠሮ ይይዛል፡፡ ባገኛትም ጊዜ ስለራሱ ብዙ ይነግራታል ትዳር እንዳማረው ጥሩ ሴት እንደሚፈልግ በውብ ንግግር ያሳምናታል፡፡ ትዳር ፈላጊዋ ልጅም በዚህ ትማረካለች፡፡ ውስጡን መመርመር ሌላ ነገር ማምጣት ነው ብላ ምታስበው ሴት ትዳር ፈላጊውን መቃወም እድልን እንደመጣል ትቆጥራች፡፡ ሁሉን እሺ ትላለች፡፡ ወንዱም ቅድመ ጋብቻ ሴት የምትጠናበት አንዱና ዋናው ግብረ ስጋ እንደሆነ ያምናል የምትወደው ከሆነ ይህን እንድታደርግ ግድ ይላታል ያሳምናታል፡፡ ይሄዳሉ፡፡ ሲመለሱ ግን ተዘጋግተው ነው፡፡ ተመልሶም አይደውል፡፡ ምነው ሲሉት የእግሯ ጣት አጭር ነው ይላችኃል፡፡ መንገደኛው ከሁለተኛዋ ጋር በአጋጣሚ ይገናኛል፡፡ ተመሳሳይ ንግግሮች ያደርጋሉ አዲሷ ሴት ትዳር ፈላጊውን ታምነዋለች፡፡ በሚፈልገው መንገድ ትሄድለታለች፡፡ ሲመለሱ ዝም ዝም ተባብለው ይመጣሉ፡፡ መልሶም አይደውልላት፡፡ ምነው ሲሉት ከለሯ አልማረከኝም ይላል፡፡ ይህ ሰው በየቀኑ ትዳር እየፈለገ ይውላል የፍለጋው መንገድ ተመሳሳይ ነው፡፡ ስለትዳር ብዙ ተናግሮ ያሳመናት ሴት አብራው ስለተኛች ይንቃታል፡፡ ሴቶች ሁሉ እንደዚህ ናቸው ብሎ ይፈርዳል፡፡ ጋብዟትም ከሆነ ገንዘቤን አይታ ነው ብሎ ያስባል፡፡ ይህን በመሰለ ሁኔታ ከብዙ ሴቶች ጋር ያሳለፈው ወንድ ድንግል ማግባት ይፈልጋል፡፡ ጌታ ካልፈቀደለት ሴቶች ጋር መተኛቱን እንደ መጠናናት ይቆጥራል፡፡ አጥኚው እርሱ ትክክል ነው ተጠኚዎቹ ግን ጋለሞታ ናቸው፡፡ይህ ፈሪሳዊ አስተሳሰብ ነው፡፡ ስታመነዝር አግኝተናታል ብለው ወደ ጌታ አንዲትን ሴት ባመጡ ጊዜ ብቻዋን ነበረች፡፡ዮሓ 8 ወንዱ አልተከሰሰም፡፡ ድንጋይ ለሴቷ ብቻ ነበር የተዘጋጀው፡፡ ይህም ሰው ስለሴቶች የሚሰጠው አስተያየት አስደንጋጭ ይሆንባችኃል፡፡ ምንም ሴት እንደሌለ በእግዚአብሔር ዓለም ለርሱ የሚመጥን እንደጠፋ አመንዝራ ልቡ የነገረውን ለሌሎች ያካፍላል፡፡ እሳካሁን የቆመው ሚስት አጥቶ እንደሆነ በድፍረት ይናገራል፡፡ እርሱ ግን ክብርና ፍቅር መስጠት የሚችል ልብ አጥቶ ነበር የቆመው፡፡ ማንም ያልነካትን ድንግል ሲፈልግ የራሱ ካልሆኑ ነገር ግን የብዙ ወንዶች ሚስቶች/ወደፊት/ ከሚሆኑ ሴቶች ጋር እየተኛ ነበር፡፡ ይህ ሰው ከአሰልቺ ፍለጋው በኃላ ቆይቶ የራሱ ሚስት ትኖረዋለች፡፡ ከሚስቱ ጋር እንደ መጀመሪያው መደሰት ይቸግረዋል፡፡ ያሳለፈው ብዙ ልምምድ ከፊቱ ይደቀናል፡፡ እርካታ ቢስ ይሆናል፡፡ ትዳሩን በአንካሳ ልቡ ሊመዝን ይጀምራል፡፡ ምክንያት ፈላጊ ቁጡ ይሆናል፡፡ ብዙ ጊዜ ሴቶች ስትባሉ… እያለ ሚስቱ ላይ ይፈላሰፋል፡፡ዓለም በጋለሞታ የተሞላች እንደሆነች ያስባል፡፡ ትዳር ፈላጊ የራሱን ድርሻ ብቻ መፈለግ ይኖርበታል፡፡እግዚአብሄር የሰጠው ሚስቱ እንደሆነች የሚለካበት ብዙ መንፈሳዊ ሚዛኖች እያሉት በሥጋ መንገድ መሄድን ማቆም አለበት፡፡ ሰው የራሱን ቤት የሚፈልገው የሰው ቤት እየከፈተ ንብረቱን እየበረበረ እየሰረቀ አይደለም፡፡ በመዝራት ህግ ሰው የዘራውን ያንኑ ያጭዳል የተባለውን ቃል ማስታወስ አለበት፡፡ መልካም የዘራ መልካም፣ መራር ዘራ መራር ያጭዳል፡፡ የሰው ነካ የራሱ ይነካበታል፡፡ የሰረቀ ይሰረቅበታል፡፡ ያስለቀሰ ብዙ ዘመን ሲያለቅስ ይኖራል፡፡ የረዳ ያገዘ ሲታገዝ ይኖራል፡፡ የታመነ ታማኝ ያገኛል፡፡ገላ 6፤7 ጎልማሳ መንገዱን በምን ያቀናል ቃሉን በመጠበቅ ነው፡፡ መዝ19፤9

Friday, January 10, 2014



ሰላም ለሁላችሁ፤- አንድ የህክምና ዶክተር በባህር ዳርቻ ንፋስ ሲቀበል ባህሩ ላይ የሚዋኙ ዳክዬዎች ትንሽ እንደዋኙ ፍግም ብለው እንደሚሞቱ ተመለከተ፡፡ ሁኔታውን ሲያጠና የዳክዬ በሽታ እንደያዛቸው ተረዳ፡፡ ሄዶም በቤተ ሙከራ ለወፎቹ መድሃኒት ፈለሰፈ፡  መድሃኒቱን ይዞ መጥቶ ሊሰጣቸው ሲሞክር ዳክዬዎቹ ሊቀርቡት አልቻሉም፡፡ ሲጠራቸው እየፈሩ ይሸሹ እና ይሞቱ ነበር፡፡ አይኑ እያየ ዳክዬዎቹ አለቁ፡፡ ዶክተሩም እነዚህ ዳክዬዎች ወደ እኔ መቅረብ የፈሩት አኔ አነሱን ስላልመሰልኩ ነው እኔ ዳክዬ ብሆን ኖሮ ቀርቤ አክማቸው ነበር አለ፡፡ አምላክ ለምን ሰው ሆነ ትላላችሁ? የሚሉ ሰው መሆኑም ክበሩን እንደማይመጥን የሚገምቱ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ነገር ግን አምነንበት አንድንድን በመድሃኒቱም፣ እንድንፈወስ፣እኛነታችንን የሚረዳ ጌታ በሥጋ ተገልጧል፡፡ሰው መሆኑን የትትናውን እና የፍቅሩን ውሳኔ ማመን ያጸድቃል፡፡ ጥንት በሙሴ ዘመን በሲና ተራራ በእሳት ተገልጦ ድምጹን ልንሰማ አንችልም እንሞታለን ብለን ፈርተን ሸሽተን ነበር፡፡ዛሬ ግን እኛን መስሎ በሥጋ ስለተዛመድን የልባችን አምላክ እና እውነተኛ አባት አድርገነዋል፡፡
እባካችሁ ለሌሎች ሼር አድርጉት