መዝሙር አንድ መንፈሳዊ ሃሳብ በዜማ ተዋህዶ በጆሮአችን የምንሰማው
እግዚአብሄርን የምናመልክበት፣ስለጌታችን አዳኝነት፣ ስለቅዱሳን ፣ስለቤተክርስቲያን፣ እንዲሁም ስለመንፈሳዊ ጉዳዮች ትምህርት የምናገኝበት
የጸጋ ስጦታ ነው፡፡መዝሙር ከመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን ጀምሮ ጥቅም ይሰጥ ነበር፡፡ የያዕቆብ ልጆች የኤርትራን ባህር በተዓምራት እንደተሻገሩ
የሙሴ እህት ማርያም ከበሮ ይዛ ከህዝቡ ጋ ለእግዚአብሄር ዘምረዋል፡፡ዘጸ 15፤21 ዳዊትም ታዋቂ ዘማሪና በገና ደርዳሪ ነበር፡፡
በመንፈስ ቅዱስ የሚገነዘበውንና በልቡ የሚሰማውን በመልክ አደራጅቶ ዘምሯል፡፡ማቴ 26… በሃዲስ ኪዳንም የሁላችን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ
እግር ባጠበበት ምሽት ከደቀመዛሙርቱ ጋር ከእራት በኃላ ዘምሯል፡፡ዮሐ… እነ ቅዱስ ጳውሎስም በእስር ቤት ዘምረዋል፡፡የሐዋ .ሥ
16
በኢትዮጵያም ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ቅድመ ቅዱስ ያሬድ አምልኮተ
እግዚአብሄር ይፈጸም ስለነበር መዝሙር ይኖር እንደነበር ይገመታል፡፡ ቅዱስ ያሬድ በ6ኛው ክፍለ ዘመን ሲነሳ መልክ ያለው ዜማ ከድርሰቱ
ጋር ለቤተክርስቲያን አዘጋጅቷል፡፡ያም እስከ ዛሬ ድረስ ቤተክርስቲያን በየበዓላቱ ስብሐተ እግዚአብሄር የምታቀርብበት የቁርባን ጸሎት/ቅዳሴ/
የምትጸልይበት ድንቅ ዜማዋ ሆኗል፡፡
መዝሙር በዘመናችን
ዘመናዊው ዓለም ሁልጊዜ የራሱን ቋንቋ የሚናገር ነውና በዘመናዊው ዓለም
ባሉ አማኞች ውስጥ በራሳቸው ቋንቋ የሚናገሩ ሌሎች ቤተእምነቶች በሚያዘጋጇቸው የተለያዩ መዝሙራት እየተሳቡ ከቤተክርስቲያን የሚሰደዱ
ሚሊየኖች እየበዙ ሲመጡ የቤተክርስቲያን ወጣቶች ያንን ሊተካ የሚችል በዜማ የተሰሩ መዝሙራትን በየሰንበት ትምህርት ቤቱና በካሴት
እያዘጋጁ ማቅረብ ጀመሩ፡፡ እነመሪጌታ ጸሐይ በምሳሌነት ይጠቀሳሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ብዙ ኦርቶዶክሳውያን ወደ ሌላ ቤተ እምነት
መፍለሳቸውን መተው ጀመሩ፡፡
አልፎ አልፎ በካሴት የሚዘጋጁ መዝሙራትን በተመለከተ ሁለት አመለካከቶች
ይሰማሉ፡፡ቆየት ያለውን የቅዱስ ያሬድን ዜማ ያስረሳል የሚሉ ተከራካሪዎች አሉ፡፡ዜማው ሊረሳ የሚችለው የካሴት መዝሙራት ስለመጡ
ሳይሆን በዜማው ላይ የተሾሙ ሰዎች ምዕመናንን በሚመጥን ሁኔታ ዜማውን ማስተማር ባለመቻላቸው ነው፡፡ የቅዱስ ያሬድን ዜማ በቀላሉ
ትውልዱ እንዲማረው ማድረግ የሊቃውንት ሃላፊነት ነው፡፡ ያንን ሳያደርጉ ቸል ቢሉ የካሴት መዝሙራት ኖሩም አልኖሩም ዜማው እየተረሳ
መምጣቱ አይቀርም፡፡ከዚህ ሃሳብ በተቃራኒ የቆሙት ተከራካሪዎች ደግሞ የቤተክርስቲያን አገልግሎት በቅኔ ማኅሌትና በቤተ መቅደስ ብቻ
የሚገደብ አይደለም፡፡ በስብከተ ወንጌል አዳራሾች፣ በማህበራዊ ሕይወት/በሰርግ በኃዘንና በደስታ/ እንዲሁም በተለያዩ ሥፍራዎች የሚደረገው መንፈሳዊ እንቅስቃሴ ሁሉ የቤተክርስቲያን አገልግሎት
ነው፡፡ ስለዚህም የአማርኛ መዝሙራት በአፍአ/በውጭ/ ያለውን አገልግሎት ከማጠናከር አንጻር ጉልህ ሚና አለው ይላሉ፡፡/የአማርኛ
መዝሙራት- መምህር ሰሎሞን ዘማህበረ ቅዱሳን/
የካሴት መዝሙራት
በእርግጥም የካሴትና የሰንበት ትምህርት ቤት መዝሙራት በዚህ ዘመን
መኖራቸው እንደማዕበል ባጥለቀለቁን የሌሎች ቤተ እምነት መዝሙራት ተስበው የሚወጡ አማኞች በቤተክርስቲያን እንዲቆዩ ትልቅ አስተዋጽኦ
አድርጓል፡፡እንዲሁም አማኞች ስለእምነታቸው ግዛቤ እንዲያገኙ፣ በተመስጦ ንስሃ እንዲገቡ፣ ከአምላካቸው ጋር በህሊና እንዲገናኙ፣
ሃዘንን እንዲረሱ፣ መንፈሳቸው እንዲበረታ ትልቅ እገዛ አድርገዋል፡፡በተለይም በገጠሪቱ ሃገራችን ያሉ ምዕመናን ሰባኪ የማግኘት እድል
የላቸውምና ወጣቶቹ በየሰንበት ትምህርት ቤታቸው ተሰብስበው መጽሐፍቶችን አንብበው እነዚህን መዝሙራት ዘምረው ይለያያሉ፡፡ በዚህም እምነታቸውን ጠብቀው አስጠብቀው እስካሁን ለመኖር
በቅተዋል፡፡
ብዙ አማራጭ ያላቸው በከተሞች የሚኖሩ አንዳንድ ተከራካሪዎች የካሴት
መዝሙራት ከምድረ ገጽ መጥፋት አለባቸው ዘፈኖች ናቸውና ይላሉ፡፡ ሁሉም ዝማሬ በግዕዝ ብቻ መዘመር አለበት በማለት የማይጨበጥ ክርክርና
ትግል ያስነሳሉ፡፡ ውሃው የእግዚአብሄር ስም ሲጠራበት ጸበል እንደሚሆን የግራሩ ዕጽ በስመ እግዚአብሄር ጽላት እንደሆነ እናምናለን
የሚሉ ሰዎች፤- የእግዚአብሄርን ስም አስተካክሎ የሚጠራና የሚያመሰግን፣ የእመቤታችንን ክብር የሚገልጥ መዝሙር ዘፈን ነው ማለታቸው
አለማመናቸውን ያሳይባቸዋል፡፡ሁሉ በሞላበት ከተማ የሚኖሩ እነዚህ የሞላ የምግብ ብፌ ፊት ቆሞ ይህ ስኳር ያስይዛል ይሄ ደም ግፊት…
እያሉ ምግቡን ሳይመገቡ የሚሳቀቁ ባለጠጎችን ይመስላሉ፡፡በክፍለ ሃገርና በውጭ ሃገር ያሉ ምዕመናን ቃሉን እጅግ ስለተራቡ የካሴቶችን
መውጪያ ቀን በጉጉት ይጠብቃሉ፡፡የመዝሙራቱን ቃላቶች የህይወታቸው መመሪያ ያደርጓቸዋል፡፡ በየመኪኖቻቸው ግንባር ላይ ይጽፏቸዋል፣
በቤታቸው በመኪናቸው በተንቀሳቃሽ ስልኮቻቸው ላይ ይጭኗቸዋል፡፡ ስለተጠቀሙባቸውም መዝሞሮቹ ላይ የሚቀርቡትን ቅምጥል አስተያየቶች
መስማት አይፈልጉም፡፡
በከተሞች
ያሉ ጥቂት ሰንበት ትቤቶች ትርጉሙን በሚገባ የማያውቋቸውን የግዕዝ መዝሙራት ብቻ እንዲዘምሩ የሚያደርግ ህግ ቀርጸው ይጠቀማሉ፡፡ይህ
የቤተክርስቲያንን መዝሙራት ጥቅም ያለመገንዘብ ውጤት ነው፡፡ መዝሙር የግዕዝ ቋንቋን የምንጠብቅበት አንዱ መንገድ ቢሆንም የመዝሙር
ዓላማ ግን የግዕዝን ቋንቋን መጠበቂያ ብቻ! ሳይሆን እግዚአብሄርን ማምለኪያ እና ማስተማሪያ መሆኑን መምህራኖቻቸው ማስገንዘብ ይገባቸዋል፡፡ ሌላው በካሴት መዝሙራት ላይ
የሚነሳው ክርክር ዘማሪው ገንዘብ ያገኝባቸዋል የሚል ይሆንና ከባድ ጽንፍ የሚፈጥር ሃሳብ ያመጣል፡፡እርግጥ እነዚህ መዝሙራት በገንዘብ
የሚገዙ ናቸው ምክንያቱም በዘመናዊ የሚዲያ መሳሪዎች ማለትም በሲዲ
እና በካሴት ሲሰሩ ከፍተኛ ወጪ ይወጣባቸዋል፡፡በነጋዴዎችም ስለሚከፋፈሉ የመንግስት ህጋዊ ግብር ይከፈልባቸዋል፡፡ አገልጋዩም የሙሉ
ሰዓት አገልጋይ ስለሆነ ለኑሮው የሚያስፈልገውን ጥቂት ገንዘብ ያገኝባቸዋል፡፡ መጽሐፍም የሚያበራየውን በሬ አፉን አትሰር ብሎ ይመሰክራል፡፡
የካሴት መዝሙራት የሚያስጨፍሩ ይሆኑ ይሆናል የሚል የሩቅ ፍርሃት የሚያድርባቸው
ሰዎች አልፎ አልፎ ይታያሉ፡፡ ኦርቶዶክሳውያን መዝሙራት ሁለት አይነት ናቸው፡፡ አንደኛው ያለከበሮ የሚዘመረው በበገና ወይ በመሰንቆ
ተጅቦ ቀስ ብሎ የሚፈሰው ዜማ ነው ይህ ብዙ ግዜ በንስሃ ግጥሞች የተሞላ ሲሆን ሰዎች በጸጥታ እንዲያደምጡት ሆኖ የተሰራ ነው፡፡ሁለተኛው
በከበሮ ቁጥጥር ስር የዋለ ዜማ ነው፡፡ ዜማው ግማሹ ክፍል በሽብሸባ ግማሹ ክፍል በከበሮ ድረባ የታጀበ ነው፡፡ይህ በከበሮ ሪትም
ቁጥጥር ስር ስላለ ወዴትም አይነት ስልት ሊንሸራተት አይችልም፡፡መዝሙሩ በዜማው ስልተ ቅርጽ ቢለያይም በአዘማመሩ ግን አንድ አይነት
ወጥ ሆኖ ተቀርጽዋል፡፡ አዘማመሩም የተወሰደው በማህሌት አንድ ወረብ ከተረገጠ በኃላ ሲደረብና ሲሸበሸብ የሚሰጠውን አይነት ስልት
የተከተለ ነው፡፡
መዝሙራቱ ያለባቸውን ተግዳሮት በእግዚአብሄር ቸርነት አልፈው ብዙ ርቀት
ለመጓዝ በቅተዋል፡፡ እግዚአብሄር ቅድመ ቅዱስ ዳዊት ዘማሪዎች ነበሩት፡፡ ነገር ግን አዲሱን የዳዊትን በገና አያስፈልግም አላለም፡፡
ነቢዩ ዳዊትም የዘመራቸው መዝሙራት ይበቁኛል አላለም ለኢትዮጵያ ቅዱስ ያሬድን አስነሳ በዚህም ጌትነቱን አሳየ፡፡በእርግጥ ቅዱስ
ያሬድ በዘመኑ በተነሳ ግዜ ስርዓት አበላሸ ዜማ አበላሸ ያሉ ሰዎች ብዙ ተዋግተውታል፡፡ አስረውም እንደገረፉት በታሪክ ይነገራል፡፡
ነገር ግን ቅዱሱ ዘማሪ እግዚአብሄር አብሮት ስለነበረ እና በአጼ ገብረመስቀል ዘንድ ተቀባይነት ስለነበረው ከሰማይ የተሰጠውን ጸጋ
ለትውልድ ትቶ ሊያልፍ ችሏል፡፡ቅዱስ ያሬድ በኢትዮጵያ ላሉ ዘማሪዎች ትልቅ አስተማሪ ነው በዜማዎቹ ካስተማረው በተጨማሪ ሕይወቱና
ጽናቱ ብዙ ደካሞችን አበርትቷል፡፡ ዛሬም በመዝሙር የተሾሙ ሁሉ አማራጭ ሳያቀርቡ በተለያየ አቅጣጫ ድንጋይ በሚወረውሩ ሳንባላታጣውያን
ሳይደናገጡ ጠንክሮ ቤተክርስቲያንን በማገልገል ላይ ይገኛሉ፡፡በስራዎቻቸው ላይ የሚነሱ ገንቢ ትችቶችን በቅን ልብ መቀበል መዝሙር
የበለጠ የሚጠቅም እንዲሆን ያግዛል፡፡ የባለሞያዎች በጎ እርማት የካሴትን መዝሙራት ጥራት ወደ በለጠ ደረጃ ሊያመጣ ይችላል፡፡ ይቀጥላል
እባካችሁ ለሌሎች ሼር አድርጉት